የፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ “እኛ እና እነሱ” ንግግር!

Published by Ayele Gelan on

የአዲስ አበባ ከተማን 133ኛ ዓመት የምስረታ መታሰቢያ በዓልን ምክንያት በማድረግ ህዳር 19 ቀን 2012 ዓ.ም በተሰናዳው ዝግጅት ላይ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ንግግር አድርጎ ነበር።  የኦሮሞ ወጣቶችን በመወረፍ ነበር የጀመረው! ምስጋና ብጤም አከለበት፣ “ይህንን ትግል ስላገዙ አለ”! ትግሉን እሱ እየመራው፣ ቄሮ/ቀሬ እያገዙት መሆኑ ነው እንግዴህ! በኦሮሞ ወጣቶች መስዋእትነት ነጻ ወጥቶ ሀገሩ እንደልገባ ሁሉ!

ያ እንዳለ ሆኖ፣ የፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋን ንግግር እጅግ አወዛጋቢ ሆኖ ነው ያገኘሁት፣ በሌሎች የተለያዩ ምክኛቶች!  እናም ይህችን አጭር ጽሁፍ አዘጋጀሁ።  በመጀመሪያ ደረጃ ከአንድ አንጋፋ ፖለቲከኛ የማይጠበቅ ንግግር ነው።

ጀምሮ እስከምጨርስ ድረስ፣ “እኛ እና እነሱ” የምል ሀረግ ደጋግሞ ተጠቅሟል። ይህ አባባል፣ በተለይ አሁን ኢትዮጵያ ካለችበት ሁኔታ አንጻር ሲታይ ከአንድ በሳል አንጋፋ ፖለቲከኛና ምሁር አይጠበቅም።  ይሄ ከፋፋይነት ብለን በቀላሉ የምናልፈው ጉዳይ ብቻም አይደለም፣ ጠብ አጫርነትም ጭምር እንጂ!  ከዚያም አልፎ “የጨበጣ ትግል፣ እነሱ ጨበጣ ከፈለጉ ሌላውም ወደ ጨበጣ የማይገባበት ሁኔታ አይኖርም” አለ። እዚህ ላይ የአዲስ አበባ ወጣቶችን ለግጭት እየጋበዘ አይደለም ለማለት አይቻልም።

“አዲስ አበባ የማን ነች?” ብሎ ማለት “ኒውዮርክ የማን ነች” እንደማለት ነው ብሎ አለ።  “አዲስ አበባ የኦሮሞ ነች!” የምለውን በሚሊዮን የምቆጠር የኦሮሞ ህዝብ በገሃድ ሲሳደብ ደግም፣ እንዲህ ነው ያለው፡ “ኒውዮርክ የማን ነች” ብሎ ሰው ቢጠይቅ “ይሄ የማን ጦጣ ነው ይሉታል”!  እንግዲህ የአዲስ አበባን ጥያቄ የምያነሳ ሰው ሁሉ፣ ሰው ሳይሆን፣ ጦጣ ተብሎ ሊፈረጅ ነው ማለት ነው። በእድሜ ገፋ ያለ ትልቅ ሰው እንዴት እንዲህ የወረደ የዱሪዬ ቋንቋ ለመጠቀም እንደምመርጥ አይገባኝም።

ይቀጥልና የኦሮሞን ህዝብ ሁኔታ ከአሜሪካ ሬድ ኢንዲአንስ ጋር ያወዳድራል።  ልክ እነሱ ኒውዮርክ የኛ ነው ለማለት እንዳበቃለት አርጎ ያነጻጽራል። በዚህ አይነት የተዛባ አመለካከት ነው እንግዲህ ሀገር ለመምራት ደፋ ቀና የምባለው!

“አዲስ አበባን ማን ያስተዳድራታል?” የሚለውም ጥያቄ ለፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ  አሲቂኝ ጥያቄ ነው።  መልሱ የአዲስ አበባ ህዝብ የመረጠው ስለመሆኑ ከመቶ በመቶ በላይ እርግጠኛ ሆኖ ይናገራል።  በሱ አስተያየት ይህ ጉዳዩ ጥቁር እና ነጭ ነው።  ሌላ ቀለም የለበትም።

ይሄ ሰው ምን አይነት መጽሃፍ እንደምያነብ አላውቅም። እዚያ ኒውዮርክ ዘሎ ከመሄድ ይልቅ በቅርባችን ያለችው ብራሰልስ በምን መልኩ እንደምትተዳዳርስ ለምን ለማንሳት አልፈለገም?  ለመሆኑ በአለማችን ካሉት ታላላቅ ከተሞች፣ የኒውዮርክ አይነት አስተዳደር ያላቸው እጅግ ጥቂት መሆናቸውን ይሄ ሰው ያውቅ ይሆን? 

ከተሞች ብቅ የምሉት የተወሰነ ህዝብ የሰፈረበት አካባቢ ውስጥ ነው።  ከተማው እዚያ ውስጥ ስለተከሰተ ብቻ፣ በፊት እዚያ ቦታ ላይና ዙሪያውን የነበረው ህዝብ በቦታው ላይ ያለው የባለቤትለት ጥያቄ እንዲሁ በዘፈቀደ አይፋቅም። 

በዚህ ምክኛት ከሞላ ጎደል ሁሉም የዓለም ከተሞች ከተከሰቱበት ቦታ ህዝብ ጋር የምያስተሳስር አስተዳደራዊ መዋቅር ይፈጠርና በዚያ ህግ ይገዛሉ።  የፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ እርግጠኝነት ከግድ የለሽነት ጋር የተቀላቀለ ግብዝነት እና አላዋቂነት ላይ የተመሰረተ ይመስለኛል። 

ባይሆንማ ኖሮ፣ እንዲህ ደረት ወጥሮ እርግጠኛ ሆኖ ከመናገር በፊት፣ ጊዜ ወስዶ፣ ለመሆኑ የዓለም ትላልቅና መካክለኛ ከተሞች አስተዳደር መዋቅር (governance structure) ምን ይምስላል?  ስንቶቹ ናቸው ሙሉ በሙሉ ራሳቸውን ችለው ተወካይ መርጠው የምተዳደሩት?  ለምንስ አብዛኛዎቹ እኔ እንደማስበው ራሳቸውን ነጥለው ማስተዳደርን ሳይሆን በታቀፉበት ከልል ስር መተዳደርን አማራጭ አርገው ወሰዱት?   

ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ አዲስ አበባን ለማስተዳደር እጅግ የቋመጠ ይመስላል።  ነገር ግን ክላይ ለጠቀስኳቸው ጥያቄዎች መልስ በመፈለግና ጥናት በማድረግ ራሱን ብቁ ለማድረግ የጣረ መስሎ አይታየኝም።  አቅሙንና ችሎታውን አለው፣ ስጀመር የዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር ነው።  ግን ማን አለብኝነትና ግብዝነቱ ብሶበት ነው እንጂ!  ለነገሩ ኢትዮጵያ ነው ያለው፣ ማወቅና መጠንቀቅ የግድ አይደለም ሀገር ለመረከብ!

 የብርሃኑ ነጋ የለበጣ ንግግር፣ ቀስ እያለ ወደ አስቂኝነት እያደላ ሄደ።  አዲስ አበባን ከተረከብኩ በኋላ ከነሱ (ዙሪያችን ካሉት) አካላት ጋር መነጋገራችን የግድ ነው፣ ቆሻሻ መጣል አለብን፣  አዲስ አበባ ማደግ (horizontally) መስፋቷ የግድ ነው።  ለዚህ ስንል፣ ለራሳችን ብለን … እያለ የ“እኛ እና እነሱ” ድስኩሩን ቀጠለበት።

ለመሆኑ አዲስ አበባ የጎዮሽ እድገቷ እንዳከተመ እንኳን አልተገነዘበም ማለት ነው፣ እንዴት ነው ነገሩ ጎበዝ? ምን ቢሆን ነው ይህን ያህል ባይተዋር የምኮነው?


Leave a comment:

Your email address will not be published. Required fields are marked *


CAPTCHA Image